በቦስተን ደብረ መንክራት ቅዱስ ገብርኤል ወልደታ ማርያም ቤተ ክርስትያን ፍሬ ሃይማኖት ሰንበት ትምህርት ቤት
ሰንበት ትምህርት ቤት ማለት የጾታና የእድሜ ልዩነት ሳታደርግ ክርስቲያኖች በዕለተ ሰንበትና በዓበይት በዓላት በተጨማሪም በአመች ጊዜ ሁሉ እምነቷንና ሥርዓቷን ሚማሩባት መንፈሳዊት ትምህርት ቤት ማለት ነው፡፡
የሰንበት ት/ቤት አባላት ማለት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ትምህርተ ሃይማኖትና ሥርዓት የሚማሩ እና እንዲሁም በአገልግሎት የሚሳተፉ የወጣት ወንዶችና ሴቶች ስብስብ ማለት ነው፡፡
የሰንበት ት/ቤቱ አላማና ተግባር
- የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እምነትና ሥርዓት ሳይለወጥ ከትውልድ ወደ ትውልድ እንዲተላለፍ ለማድረግ ይቻል ዘንድ አደራጅቶና ወቅቱ በሚፈቅደው ይዘት አመቻችቶ ትምህርተ ሃይማኖት ለሁሉም እንዲዳረስ ለማድረግና ሰማያዊ ርስትን የሚወርሱበትን የእግዚአብሔርን ቃል እንዲያውቁ ማድረግ፡፡
- ማንኛውም የቤተክርስቲያኒቷ እምነት ተከታይ የሆነ ምእመናን ሁሉ ሃይማኖቱንና ሥርዓቱን በውል እንዲያውቁና እንዲረዱ ማድረግ፡፡
- ወጣቱ ትውልድ በሰንበት ት/ቤት ውስጥ አባል ሆኖ ቤተ ክርስቲያንን በቅንነት እንዲያገለግልና በአበው እግር ሥር ተተኪ የሚሆኑ ሰዎችን ማፍራት እንዲሁም የቤተክርስቲያኒቷን ሥርዓት ሳይበረዝና ሳይደለዝ የቀደመ እምነቷን ይዛ ለተተኪው ትውልድ ማስረከብ እንዲችል ማድረግ፡፡
- ሕጻናትና ወጣቶች የቤተ ክርስቲያንን ሕግና ቃለ እግዚአብሔርን ተምረው ወላጆቻቸውንና ታላላቆቻቸውን አክባሪ እንዲሆኑና በአጠቃላይ ለወገን መልካም ዜጎች እንዲሆኑ ማድረግ፡፡
- የሰንበት ት/ቤቱ አባላት ባላቸው እውቀት፣ ገንዘብና ጉልበት ክርስቲያናዊ አገልግሎት እንዲያበረክቱ ማድረግና ማበረታታት።
- የሚመለከታቸውን የቤተ ክርስቲያኒቱን የሰበካ ጉባዔውን አስተዳደር በማስፈቀድና በማማከር ቃለ እግዚአብሔር በበራሪ ጽሑፎች፣ በካሴቶችና በመሳሰሉት እንዲስፋፋ ማድረግ::
በቦስተን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በደብረ መንክራት ቅዱስ ገብርኤል ወልደታ ማርያም ቤተክርስቲያን የፍሬ ሃይማኖት ሰንበት ትምህርት ቤት ቤተክርስትያኗ ከተመሰረተችበት ጊዜ ጀምሮ የተለያዩ አገልግሎቶችን በመፈጸም ላይ ይገኛል
እንግዲህ ከዚህ በላይ የተጠቀሱትን ዓላማ ለማሳካት የፍሬ ሃይማኖት ሰንበት ትምህርት ቤት ለጊዜው ከዚህ በታች የተዘረዘሩ ክፍሎችን ከነተጠሪያቸው በማዋቀር አገልግሎቱን በመፈጸም ላይ ይገኛል
- ጽህፈት ቤት
- ሰብሳቢ
- ምክትል ሰብሳቢ
- ጸሐፊ
- የትምህርት ክፍል
- የግንኙነት (የአባላት ክትትል ክፍል)
- የመዝሙር ክፍል
- የንብረት ክፍል
- የሂሳብ ክፍል
